ሰበር ዜና: ትናንት ተቋርጦ የነበረው ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም መግቢያ ፈተና ከሰኔ 27 እስከ 30 ይሰጣል


43a2ab17b9855d2dae648997ab795fed_Lትናንት ተቋርጦ የነበረው የ12ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና የሚሰጥበትን ቀን የትምህርት ሚኒስቴር ይፋ አደረገ።

የትምህርት ሚኒስትሩ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በተለይም ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለፁት፥ ከሰኔ 27 ጀምሮ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2008 ዓመተ ምህረት ድረስ ፈተናው ይሰጣል።

የ12ኛ ክፍል ፈተና ኮድ 14 የእንግሊዝኛ ፈተና መውጣቱ በመረጋገጡ እና ሌሎች ፈተናዎች ላለመውጣታቸው ምንም ዓይነት ማረጋገጫ ባለመኖሩ እንዲሰረዝ መደረጉን ትናንት ሚኒስትሩ መግለፃቸው ይታወሳል።

አሁን የሚሰጠው የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ዝግጅት እና አሰጣጥ በከፍተኛ ጥንቃቄ እና ጥበቃ የሚከናወን እንደሚሆንም ነው ሚኒስትሩ የገለፁት።

ሀገር አቀፍ ፈተናው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጥናትና ምርምር ማዕከል አማካኝነት በከፍተኛ ጥንቃቄ እንደሚዘጋጅ ያስረዱት አቶ ሽፈራው፥ ባለሙያዎቹ ተፈታኝ የስጋ ዘመድ እንደሌላቸው ተረጋግጦ በፈተና ዝግጅት እንዲሳተፉ እንደሚደረግም ተናግረዋል።

ፈተናው በመቀጠልም በተደራጀ እና ምስጢራዊነቱን በጠበቀ መልኩ የህትመትና የስርጭት ስራው እንደሚከናወንም ነው ያረጋገጡት።

በፈተና ስርቆት ተግባሩ ላይ የተሳተፉ አካላትም ህጉ በሚፈቅደው መሰረት አስፈላጊውን ማጣራት በማካሄድ ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ እንደሚደረግም ሚኒስትሩ ገልፀዋል።

አቶ ሽፈራው ተማሪዎች በቀጣይ አንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለፈተና ዝግጀት በማድረግ በተጠቀሰው ጊዜ ፈተናውን እንዲወስዱ አሳስበዋል።

በሳሙኤል ዳኛቸው